Friday, October 15, 2010

Very deep, very deep is the well of the past. Should we not call it bottomless? Thomas Mann

ታሪክ አንድ በሁለተኛ ዙር ስትጎበኘን
ᎀኤል ሽፈራው/ዳላስ

ዛሬ አካባቢያችንን በተመለከተ ትንሽ ልንል ተነስተናል። ታሪክ እራሱን ይደግማል እንዲሉ ዛሬ በዚህ በዳላስ ፎርትወርዝ አካባቢ የምናየው ሁኔታ ወያኔ ባህርዳርንና ጎንደርን በያዘበት ወቅት የነበረውን ደጋሚ ሆኖ ስላገኘነው ባይገርመንም የተዋንያኑ ምሥል ግን ድባብ ሰጥቶናል።

ነገሩ እንዲህ ነው። ያኔ በ1989-90 እ.ኤ.አ አንድ መድረክ የሚባል ስብስብ በአገራችን አንዣቦ በነበረው አደጋ ዙሪያ ሁሉንም ዜጋ አገናኝቶ ሊያወያይ የሚችል በሚል ይፈጠራል። ይህን መድረክ በጊዜው ለመጠቀም የታሰበው አገራችን ወዳጅ አልባ በመሆን፤ ምእራባውያኑ ከከባቢ የአረብ መንግስታት ጋር በመሆን የታሰበውን የሰሜን ግዛቷን ገንጥሎ ለመስጠት የተረባረቡበት ጊዜ በመሆኑ። በአገር ውስጥ አለሁ ይል የነበረው የመንግስቱ ሐይለማርያም አንባገነን መንግስት ከወዳጁ የሶቭየት ሕብረት ተለያይቶ ብቻውን የሚንጠራወዝበትና ሕዝቡ በጦርነት የሚናጥበት ብሎም የሰሜን ተገንጣዮች በድል አድራጊነት የሚገሰግሱበት ወቅት ስለነበር። በውጭ የሚኖረውን ኢትዮጵያዊ ከአገሩና ከሕዝቡ ጎን እንዲቆም ለማስተባበር ታስቦ ነበር የተመሰረተ። ውሎ ሳያድር አንዳንዶች አጥንትና ደም ቆጥረው ለሕዝብና ለአገር ሳይሆን በመገስገስ ላይ ለነበሩት ሊያግዝ የሚችል እርምጃወች መውሰድ ጀመሩ። የለም ይህ አይሆንም። ላገር ለወገን የሚጠቅም አይደለም በሚል በዚያ የአመራር ኮሚቴ ውስጥ የነበሩ ቢሞክሩም ድምጻቸው በብዙሀኑ ተዋጠ። ትቂቶቹ እንዴውም ሚዛን በማየት ድምጽ ሰጭ ሆነው አረፉትና የወያኔና ሻብያ ደጋፊወች የበላይነቱን ወሰዱ።

በዚያ አስቸጋሪ ወቅት፤ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ድምጽ መታፈን በውጭ ለድል አድራጊወች አንፋሽ አጎንባሽ መባዛት በጊዜው ለቁርጥ ኢትዮጵያውያን ተስፋ አስቆራጭና አሳዛኝም ነበር። አገር ወዳድ ነን ይሉ የነበሩ እዚያ የወያኔ፣ ሻቢያ፣ ኦነግ ደጋፊ ከነበሩትና ብዙሐን መሆን ከቻሉት ጋር ድምጽ በመስጠት ለታሪክ የማንረሳው በጊዜው ወያኔን ከአሜሪካን መንግስት ጋር አገናኝ የነበሩትን ዶክተር ደጃዝማች ዘውዴ ገ/ስላሴን በእንግድነት ጋበዙ። አይሆንም ብሎ የተከራከረ አንድ ድምጽ እንደነበር ዛሬም የዚያን ጊዜ የውይይት ሚኒት ከጃችን አለ።

በሚቀጥለው የኦነጉን አመራር፣ ከሻብያ የውጭ ግንኙነት ዋና ሐላፊ ጋር በመጨመር አንድ ኢትዮጵያዊ ዶክተር መስፍን አረያን አካተው ስብሰባ ተጠራ። ዳግም ውርደት እንዲሉ ዶክተር መስፍን አርያ በሁለቱ ተቧዳኝ ጸረ ኢትዮጵያ ምሁራን ተሰደበ። ኢትዮጵያውያን ተጠርተው ተሰድበው ወደቤታቸው ተመለሱ። ወደስብሰባው የመጡ ኢትዮጵያውያን፣ ከወያኔ፣ ሻቢያ፣ ኦነግ ጥምር ደጋፊወች በቀር ስብሰባውን ጥለው ሄዱ።

በኢትዮጵያ ስም የተቋቋመ የውይይት መድረክ ለጠላት አንባሳደር ሆኖ ሲያገለግል አይተናል። ያኔ ያገሪቱን አንድነት እንደግፋለን ያሉት ድምጽ ለጸረአንድነቶች እንደሰጡም ታዝበናል። ዛሬ ዳግም በተመሳሳይ ተዋንያን የዚያን ጊዜ ጉድ እየተደገመ ስናይ እንዴት በሁለት አስርት አመታት በተመሳሳይ ተዋንያን ታሪክ እራሷን ደገመች ማለታችን አልቀረም።

በአሁኑ ጊዜ የአማራ ልማት ማሕበር (አ.ል.ማ) ስር ተደራጅተው ኢትዮጵያውያንን በዚህ ድርጅት ስር ለማሰባሰብና እጅ እንዲሰጡ ደፋ ቀና የሚሉት፣ ሌላውን በተለየም ይቃወመናል ብለው ያሰቡትን ሁሉ እየጠሩ መጠየቅ እንደጀመሩም ስንሰማ ታዝበናል። አልፈው ተርፈው በወያኔ ተዘይዶ የቀረበልንን ድርጅት የሚቃወሙ ሁሉ ፖለቲከኞች ናቸው ሲሉም ይደመጣሉ። ፖእለቲካ ያውም የዘር በጠላት የታሰበና የተደራጀ እየሰሩ ለአገር ተቆርቋሪ  የሆኑ ወገኖችን ሁሉ ፖለቲከኛ ማለት ለማደናቆር እንደሆነ ለኛ ግልጽ ነው። ታሪክ እራሷን ትደግማለች ያልንም ለዚህ ነበር። ያኔ ወያኔን፣ ሻብያን እና ኦነግን እየደገፉ ለአገር ለወገን ተቆርቋሪ ወገኖችን ፖለቲከኞች ብለው ያሳጡ እንደነበር ይታወሰናል።

ተመሳሳይ ግለሰቦች ትናንት ጸረ ኢትዮጵያ ሐይሎችን ደግፈው ዛሬ ደግሞ ወደ መለስ በመጠቃለል አ.ል.ማን መስርተው እየተንቀሳቀሱ ስናይ ዳግም ታሪክ መሰራቱን በትዝብ እያስታወስን ነው። ኦ.ነ.ግ ዛሬ እንደያኔው ከወያኔ ጋር ባለመሆኑ እነዚያ ደጋፊወቹ አሁንም ይደግፉት ወይን ይቃወሙት አናውቅም። ሆኖም ያው ከመሀበሩ ያልተለዩ መሆኑን ግን አስተውለናል።

ወያኔ/ኢሕአዴግ ከምንጊዜውም በተሻለ ከፍተኛ የመንቀሳቀስና የመደራጀት ሙከራውን በውጭ ቀጥሏል። በዋሽንግተን ዲሲና በኒውዮር የተደረጉ የድጋፍ ሰልፎች ከምንም የመጡ አልነበሩም። በከተማችንም ተመሳሳይ እንቅስቃሴ እየተካሔደ ነው። ለአመታት የተገነቡ፣ የተደራጁ ተቋማትን በውድም በግድ ለመንጠቅም እየተካሄደ ያለው ሴር ላለማየት ላልፈለጉ ይደበቅ እንደሁ እንጅ። ገሐድ የወጣ ያደባባይ ሚስጥር ሆኗል።

በሰሜን አሜሪካ፣ አውሮፓ ከተሞች በውጭ ፋይናንሱ ሞሐመድ አላሙዲን አማካኝነት የኢትዮጵያውያን ተቋማት እንደ የሰሜን አሜሪካ ስፖርት ፌደሬሽን፣ ኮሚውኒቲና አብያተ ክርስቲያናትን ለመንጠቅ ወይም በሰላም በቁጥጥር ለማስገባት የሚደረገው ደባ አሉባልታ ሳይሆን ገሐድ እንቅስቃሴ ነው። ተስፋ ቆራጮችም በዚህ ተግባር ደባል መሆን ሲዳዱ፣ ለአንባገነኑ መለስ ላሜ ወለደች እንዲል ሆኗል። ይህ ተንኮለኛና መሰሪ አንቱ የተባሉ በእድሜም ሆነ በኑሮ መልካም ሁኔታ ላይ ያሉትን በተለያየ መልክ ወደሱ ለማስገባት ሁኔታውም አጋዥ ሆኖ አግኝቶታል። ዛሬ አትልፉ የወያኔ መንግስት አይነቃነቅም። አርፋችሁ ተቀመጡ የሚለው በአንድና ሁለት መጨመሩን ስናይ በትዝብት እንጅ በብስጭት እንዳልሆነ ይታወቅ። ምክንያቱም እውነት የማታ ማታ አሸናፊ ናትና።

የኛን ጩኸት ነጥቀው ተበደልን ሲሉ። በኛ ላይ ፖለቲካ ያውም የዘር እየሰሩ፣ ለሰበአዊ መብት፣ ለእኩልነት፣ ለአገር አንድነት የሚቆረቆሩ ወገኖችን ፖለቲከኞች ሲሉ ስንሰማ ጅራፍ እራሱ ገርፎ እዲሉ ተቸግረናል። እነኝህ ልብ አውልቅ ግለኞች እነሱ በልተው እስካደሩ፤ ሌላው ቢደፋ ጉዳያቸው እንዳልሆነ እውቅ ስራቸው አሳይቶናል። ከአናሳው የመጡ ጠባቦች ሰጥ ለጥ አርገው ያለልዋጭ እየገዙ ተዋቸው ሲሉ፣ ያዛኝ ቅቤ አንጓች መሆናቸውን ያሳዩናል። በየ አራት አመቱ በሚለወጥ የሕዝብ ውክልና ባለውና በገለልተኛ ዳኝነት በጋራ ሕገመንግስት በሚተዳደር አገር እየኖሩ መለስ ለዘላለም ይግዛ ይሉናል።

ታሪክ እራሷን ትደግማለች እንዲሉ በየከተሞችና በዚህ በምንኖርበት ቀበሌም ከ 20 አመታት በፊት ያየነውን ሲደገም በመታዘባችን እንሆ ታሪክ አንድ ሌላ ዙር በተመሳሳይ ተዋንያን አብስራናለች። ለሁሉም ሕዝባችን ዴሞክራሲ ይፈልጋል፣ እኩልነትና ፍጹም ነጻ ሆኖ እንዲኖር ይመኛል። ሕዝባችንና አገራችን የቅድመስልጣኔ ቁንጮ እንጅ እንደሌሎች የአውሮፓ ቅኝ ገዥ የፈጠረን አይደለንም። በነጻ የመኖርና የማለፍ መብቱ እንዲከበር ላለፉት አርባ አመታት ታግሏል። እውን እስኪሆንም ትግሉ ይቀጥላል። ዴሞክራሲ አይሆንህም የሚሉትን፣ ነጻነትን መለስ ሰጠህ የሚሉትን ለታሪክ ብሎ ትግሉን ይቀጥላል።

መልካም ሰንበት

Wednesday, October 6, 2010

እልም ነው፣ ጭልጥ ነው፤ ውሃ አይላመጥም። ወዳጅ ጠላት ላይሆን............የተከፋ አንጎራጓሪ

የወይዘሪት ብርቱካን ሚዲቅሳ መፈታት ውብ ዜና
ᎀኤል ሽፈራው/ዳላስ

ዛሬ መስከረም 26 ቀን 2003 ዓ.ም በእምነበለ ፍርድ ለ 20 ወራት በእስር የቆየችው ታጋይ ወጣት ወ/ሪት ብርቲካን ሚዲቅሳ ከስድስት አመት ልጇና ከአዛውንት እናቷ ተቀላቅላለች። ከዘመን ዘመን ግፍ ተዘርቶ ግፍ የሚመረትባቷ ኢትዮጵያ አሁንም ባላቋረጠ የግፍ ጅረት ትንገላታለች። ወ/ሪት ብርቱካን ከሌሎች የቅንጅት አመራር አባላት ጋር በምርጫ 97 ማግስት ታስራ ሁለት አመት በእስር ቆይታ በተለቀቀች አመት እንኳን ሳይሞላ ዳግም ያለምንም ምክንያት እንደገና ወህኒ ተወርውራ ሌላ ለሁለት አመት ፈሪ ማስቆጠሯ ለሁላችንም ያሳዝናል።

ወይዘሪት ብርቱካን ለሕዝብ ልእልና፣ ለአገር አንድነትና ለዴሞክራሲ ስትል የተቀበለችው ግፍና መከራ ለተከታይ ትውልዶች አኩሪና አንጸባራቂ ገድል ነው እንላለን።

ወያኔ/ኢሕአዴግ አዲስ አበባን ሲቆጣጠር የአገሪቱ እስር ቤቶች አፋቸውን ከፍተው ሳይሆን የጠበቁት በንጹሀን ተሞልተው ነበር ያገኛቸው። ከሊቁ ደቀመዝሙሩ እንዲሉ በዘመነ ወያኔ በየከተማው ያሉና የነበሩ ህጋዊ እስርቤቶች ሞልተውና ተትረፍርፈው፤ ተጨማሪ ማጎሪያ ካምፖችን ጨምሮ በአስርና በመቶ ሽሕወች የሚቆጠሩ ዜጎችን አጉሯል። ወይዘሪት ብርቱካን የህግ ትምህርቷን አጠናቃ በአገሯ የዳኝነት ሙያ ተሰማርታ ስታገለግል ከቆየች በኋላ፤ ዘረኛው መንግስት በዜጎች ላይ በሕግ ስም የሚካሄደውን ወከባ፣ እስራትና ግድያ በአይኗ አይታ፣ በእጇ ዳሳ በመገንዘቧ፤ ኢፍትሀዊ ስርአት ባለባት ኢትዮጵያ የዳኝነት ወንበሯን ይዛ ለመቆየት ሕሊናዋ ስላልቻለ። የሕግ የበላይነትን ለማስከበር በሰላም አገር ውስጥ ከሚታገሉ ሐይሎች ጋር ተቀላቅላ አኩሪ ገድል አስመዝግባለች።

ወይዘሪት ብርቱካን ታዋቂና ምርጫ 97 ከወለዳቸው ታጋይ ወጣቶች አንዷ በመሆኗ። የእሷን በግፍ መጋዝ አስመልክቶ በውጭና በአገር ውስጥ ከፍተኛ የትፈታ ትግል ተደርጓል። የእርዳታ ሰጭ ድርጅቶችም ሆኑ፤ የወያኔውን መንግስት እንደግፋለን የሚሉ መንግስታት ይህን የእሷን መታሰር አስመልክቶ በሰበአዊ መብት ተሟጋቾች ይቀርብ የነበረውን የትፈታ ጥያቄ ችላ ሊሉት አልቻሉም። በመሆኑም የወያኔውን መሪ መለሰ ዜናዊን መጎትጎታቸው አልቀረም። በቅርቡ በኒውዮርክ የኮሎምቢያ ዩኒቨርስቲ ጉዱን መለስ ዜናዊን በጋበዘበት ወቅት ለዩኒቨርስቲው ፕሬዜዳንት ያጋጠመው አለም አቀፍ ጩኸት የዚህ ግፊት አንዱ አካል ነበር። መለስ ኮሎምቢያ በመጣበት ወቅት ከኢራኑ ፕሬዚዳንት አህመዳጃድ የበለጠ ተቃውሞ በአዳራሽ ውስጥም ሆነ በግቢው እንደደረሰበት ታውቋል። ይህን ግፊትና ሐፍረት ለመሸፈን ሲል ታጋይዋን ይቅርታ ጠየቀች ለማለት ተገዷል። ብርቱካንን ከመፍታት አዜብን መፍታት ይቀለኛል እንዳላለ። የአለማቀፍ ግፊትና በየሄደበት ያጋጠመውን ወከባ መቋቋም ግን ሊሆንለት አልቻለም። ትግሉ ይቀጥላል። በእየእስር ቤቱ አሁንም በግፍ የታሰሩ ኢትዮጵያውያንን በመደገፍ አለማቀፋዊው የተቃውሞ ሰልፍና አቤቱታ ይቀጥላል። 80 ሚሊዮን ሕዝባችን ነጻ እስኪወጣ ቀጣይ ትግል ከፊት ለኢትዮጵያ ታጋዮች በውስጥም በውጭም ይጠብቃቸዋል።

ለዚህች አገር ክብር፣ ለሕዝቧ ነጻነትና ለሕግ የበላይነት ሲሉ የትናንት አንባገነኖችን የታገሉ የወያኒንም ዘረኛና ጠባብ መንግስት በመታገል ላይ እያሉ ዳብዛቸው የጠፋ አያሌ እውቅ የትውልዳችን ታጋዮች ዛሬም ከእስር አልተፈቱም። ወያኔ የኢሕአፓ መሪወችንና ታጋዮችን የት እንዳደረሰ እንኳን አልተነፈሰም። እነዚያ ታጋዮች ዛሬም በወያኔ የጉድጓድ እስር ቤት ባዶ ስድስት በሚባል በትግራይ ክፍለሀገር በተሰራ፤ ወያኔወች በረሐ በነበሩበት ጊዜ ለአገር ተቆርቋሪ የነበሩ የትግራይ ተወላጆችን አሰቃይተው የፈጁበት እስር ቤት ዛሬም ላገር አንድነት፣ ለሕዝብ እኩልነትና ዴሞክራሲ በኢትዮጵያ በማለት ግንባራቸውን ባላጠፉ ታጋዮች ተሞልቷል።

ታጋይዋ አበራሽ በርታና፣ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ጀምሮ 1956 ዓ. ም በትግሉ ጎራ ተሰልፎ የወጣት እድሜውን በበረሀ ያሳለፈው ጸጋዬ ገ/መድሕን (ደብተራው) ይስሐቅ ደብረ ጺዮን፣ ተስፋየ ከበደ፣ ስጦታው ሐሰን፣ ወንዱ ሲራክ፣ አበበ አይነኩሉና ሌሎች ታጋዮችም ላለፉት 20 አመታት በጉድጓድ እስር ይገኛሉ።

አቶ አበራ የማነአብ በ1994 እ ኤ አ የአማራጭ ሐይሎችን የሰላምና የእርቅ አላማን ይዞ አዲስ አበባ በመጓዝ ከቦሌ ያውሮፕላን ማረፊያ ተይዞ ላለፉት 16 አመታት በእስር ላይ ይገኛል። ይህን ታጋይ ዜጋ የወያኔው ፍርድ ቤት እንኳን ፈቶ ካሰናበተው በኋላ በመለስና ተባባሪወቹ መልሶ ወደእስር እዲወረወር ተደርጓል።

ወያኔ አዲስ አበባን ሲቆጣጠር በደቡባዊና በምስራቅ ክፍለሐገራት ከትውልድ ትውልድ የኖሩ ዜጎችን፣ በነፍጠኝነት፣ በትምክሕተኝነት በመወንጀልና፤ ነዋሪውን በመቀስቀስ፤ ወገኖቻችን በገደል እዲወረወሩ አድርጓል፣ አስደርጓል።

ይህን ግፍ የተቃወሙት ታዋቂው ሐኪም ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ ለምን የሕዝብ ግፍን እያዩ ዝም አላሉም በሚል ቂመኛና በቀልተኛ በሆነ የወያኔ ሴራ ተይዘው በእምነበለ ፍርድ፣ ሕክምና እንዳያገኙ በመደረግ ለሞት ተዳርገዋል። ታጋዩ ግንባራቸውን ሳያጥፉ ከዘረኛ ወያኔወች ምንም አይነት የይቅርታ ቃል ሳይተነፍሱ ሕይወታቸውን አሳልፈዋል። ወያኔ በዘረኝነት ተወልዶ በዘረኝነት ያደገ ቂመኛ ድርጅት በመሆኑ። አላማ ተግባሬ ብሎ ትግል ሲጀምር በጸረ አማራነት ሲሆን። ያባሕርይው ስልጣን ከያዘ 20 አመታት በኋላም አልበረደም። አነጣጥሮ የተነሳበትን አላማውን አገር በመቁረስና ለባእዳን በመቸብቸብም የቂምና የበቀል ቋያው መግለጫ ሲሆን አሁንም ድረስ አልበረደለትም። ዛሬ ያሰበው ኢትዮጵያዊነትና ኢትዮጵያዊ ብሄርተኝነት ሊጠፋ ባለመቻሉ። የእውር ድንብሩን ከወዲያ ወዲህ በመምዘግዘግ፤ በኦሮሞኛ ተናጋሪ ዜጋ ላይ የከፈተው ጦርነት በአስርና በመቶ ሽሕወች ወደእስርና ስደት ወርውሯል። ትናንት በአማራ ሲዘምት ዝም በመባሉ ዛሬ በኦሮሞ ወገን በኦነግነት እየከሰሰ ሲዘምት አናጥሎ የማጥቃት ስልት መሆኑን መገንዘብ ይገባል እንላለን።

ላለፉት ሰባትና ስምንት አመታት ኦሮምኛ ተናጋሪ ዜጎች ያለምንም ወንጀል ከየቀያቸው እየታደኑ በቃሊቲ፣ በሸዋ ሮቢትና በሌሎች ማጎሪያ ካምፖች በመታጎር በሽህወቹ የሚቆጠሩ ዜጎች በተስቦ በሽታ እንዲያልቁ ተደርጓል።

ይህን አይን ያወጣ ግፍ፣ በዜጋና ባገር ላይ የሚፈጸም ወንጀልን እንደትክክለኛ በመቁጠር ከጎኑ የቆሙ ሁሉ ሳይመሽ መገልበጡን ቢያውቁበት ምንኛ ባማረባቸው ነበር።

አለም ያወቀውን የጥቁር ዘረኛ ምግባረ ብልሹ መንግስት፤ አንዳንድ ግለሰቦች ሀብትና ንብረት እናገኛለን በማለት ደጋፊ ሆነው ስናይ፤ መለሰ ዜናዊን እንደመላክ ለማቅረብ ሲዳዱ ስንታዘብ በሐፍረትና በሐዘን ነው። ላለፉት 20 አመታት በሕዝባችን ላይ የወረደውን ግፍ የአገር መቆረስና የባእዳን መሰጠትን፤ የሐይማኖቶችን ግጭት ማራገብን ላንድም ቀን ያልኮነኑት የእምነት ቤታችንን እንዲመሩ ተሿሚውን አባ ጳውሎስንም የሚደግፉ ብጹሕ ናቸው ተቀበሉ ብለው የሚያስገድዱንንም ስናይ እንዲሁ በትዝብnና በሐዘን ነው።

ለሁሉም ዛሬ የወይዘሪት ብርቱካን መከራ ባያልቅም። ከጠባቧ የማጎሪያ ቦታ መውጣቷን ስንሰማ፤ ጡቷን ለተነጠቀችው ቃሌና ለደካማ እናቷ እንኳን ድስ ያላችሁ እንላለን። የሁሉንም በግፍ የታሰሩ። ለአመታት በባዶ ስድስት የጉድጓድ እስር ቤት ለተወረወሩ፤ ለነ አበራ የማናብ፣ ጸጋዬ ገ/መድሕን፣ ስጦታው ሐሰን፡ ወንዱ ሲራክ፣ ተስፋየ ከበደ፣ አበበ አይነኩሉ፣ አበራሽ በርታ እና አእላፍ መከራ ተቀባይ ወገኖቻችን ሁሉ ነጻነት እንድንታገል እናሳስባለን። አፋቸውን ከፍተው የሚጠብቁት የቃሊቲ፣ የሸዋ እሮቢት፣ የጊቤ፣ የትግራይ የጉድጓድ ማጎሪያወች ሁሉ የሚዘጉት ዘረኛውና አንባ ገነኑ ወያኔ ሲወገድ ነው። ለዚያም አሁንም ትግል አሁንም ድጋፍ ይጠይቃል።

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ